@ebcnewsnow · Post #52224 · 03/08/2026, 08:47 PM
የተሰበረ ተስፋ የሚጠገንበት ማዕከል ************* ለነገዋ የሴቶች ተሀድሶና ክህሎት ማበልፀጊያ ማዕከል በኢትዮጵያ በከባድ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ውስጥ ለሚገኙ ሴቶች አዲስ የሕይወት ተስፋን በመስጠት ረገድ ግንባር ቀደም ተምሳሌት ሆኖ ቀጥሏል። ማዕከሉ በተለይም በጎዳና ላይ የሚኖሩና በተለያዩ ችግሮች ውስጥ የሚገኙ ሴቶችን በዘላቂነት ለመደገፍ የሚደረገውን ሀገራዊ ጥረት በግንባር ቀደምትነት እያገዘ ይገኛል፡፡ ተቋሙ ከመጠለያ ባለፈ የተሟላ የሥነ-ልቦና ምክርና የሕክምና እርዳታን በማካተት ሴቶች በራስ መተማመን ተገንብተው ወደ ማኅበረሰቡ እንዲቀላቀሉ እያደረገ ነው። ይህ የለውጥ ጉዞ በዋነኝነት ትኩረቱን ያደረገው ሴቶች በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ሰልጥነው ራሳቸውን እንዲችሉ በማድረግ ላይ ነው። ማዕከሉ በባህል አልባሳት ስፌት፣ በምግብ ዝግጅት፣ በውበት አጠባበቅ እንዲሁም በመሠረታዊ የንግድ ሥራ አያያዝ ስልጠናዎችን በመስጠት ሰልጣኞቹን ለሥራ ዓለም ብቁ እያደረጋቸው ይገኛል። እስካሁንም በአራት ዙሮች 2 ሺህ 401 ሴቶችን በተለያዩ የሙያ ዘርፎች አሰልጥኖ ያስመረቀ ሲሆን፣ እነዚህ ተመራቂዎች በአሁኑ ወቅት ወደ ሥራው ዓለም በመቀላቀል ሕይወታቸውን መለወጥ መጀመራቸው ለሌሎች መሰል ችግር ውስጥ ላሉ ሴቶች ትልቅ አርአያ ሆኗል። በንፍታሌም እንግዳወርቅ #Ethiopia#WomenEmpowerment#SkillDevelopment#Entrepreneurship#YeNegewa#EthiopianBroadcastingCorporation