@ebcnewsnow · Post #51796 · 2026/02/19 09:17
የአቶ አማን ፍሥሐጽዮን አስከሬን የክብር ሽኝት መርሐ ግብር እየተከናወነ ነው *********** በኢትዮጵያ የግል የቴሌቭዥን ስርጭት ታሪክ ፈር ቀዳጅና ስማቸው በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰው የኢቢኤስ ቴሌቭዥን መሥራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አማን ፍሥሐጽዮን አስከሬን የክብር ሽኝት በዓድዋ ድል መታሰቢያ እየተከናወነ ይገኛል። በክብር ሽኝት መርሐ ግብሩ ላይ የአቶ አማን ፍሥሐጽዮን የሕይወት ታሪክ፣ ለኢትዮጵያ ሚዲያ ዕድገት ያበረከቱት አስተዋጽኦ እና በሥራቸው ለብዙዎች ምሳሌ የነበሩባቸው የሕይወት ምዕራፎች እየተዘከሩ ነው። አቶ አማን የኢትዮጵያን ማንነትና ባህል ከዘመናዊው የሚዲያ ቴክኖሎጂ ጋር በማቀናጀት፣ ላለፉት 18 ዓመታት በሀገሪቱ የሚዲያ ኢንዱስትሪ ላይ የማይረሳ ታሪካዊ አሻራ ያሳረፉ ስኬታማ ሥራ ፈጣሪ ነበሩ። በመታሰቢያ መርሐ ግብሩ ላይ የቤተሰብ አባላት፣ ወዳጅ ዘመዶች፣ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ አንጋፋና ወጣት ጋዜጠኞች፣ የጥበብ ሰዎች፣ አድናቂዎቻቸውና የቅርብ የሥራ ባልደረቦቻቸው ተገኝተዋል። የአቶ አማን ፍሥሐጽዮን የሥርዓተ ቀበር ዛሬ ከቀኑ 9 ሰዓት በቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ መካነ መቃብር የሚፈጸም ይሆናል። በሕይወት አበበ #EthiopianBroadcastingCorporation#Ethiopia#AmanFissehation#EBS