@ebcnewsnow · Post #53015 · 04.04.2026 г., 08:02
ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት ፓርቲ በይፋ የምርጫ ቅስቀሳውን ጀመረ *********************** በመጪው ግንቦት ወር ለሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሚወዳደረው ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት ፓርቲ ከዛሬ ጀምሮ በይፋ የምርጫ ቅስቀሳ መጀመሩን አስታውቋል። የፓርቲው ፕሬዚዳንት አቶ አብርሃም ጌጡ ፓርቲያቸው በመላ ኢትዮጵያ በሚካሄደው ምርጫ ላይ በቁርጠኝነት ለመሳተፍ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን እና የቅስቀሳ ሥራውን መጀመሩን ገልጸዋል። ምርጫ የዴሞክራሲ ሥርዓት እንዲጎለብት እና የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን ቁልፍ ሚና እንዳለው አጽንኦት የሰጡት ፕሬዚዳንቱ፣ ሕዝቡም በቀሩት ቀናት ውስጥ የመራጭነት ካርድ እንዲያወጣ፣ በምርጫው ሂደት በንቃት በመሳተፍ ለዴሞክራሲ መጎልበት የበኩሉን ሚና እንዲያኖር ጥሪ አቅርበዋል። ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት ፓርቲ የምርጫ ቅስቀሳውን በመላ ኢትዮጵያ ቤት ለቤት በመንቀሳቀስ የፓርቲውን ፖሊሲዎች እና አማራጮች ለዜጎች እንደሚያስረዳ የገለጸ ሲሆን የቅስቀሳ ሥራውን ሲያከናውን ሕዝቡ አስፈላጊውን ትብብር እና ድጋፍ እንዲያደርግለት ፓርቲው ጥሪ አቅርቧል። ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት ፓርቲ ኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)፣ አማራ ግዮናዊ ንቅናቄ (አግን)፣ እናት ፓርቲ እና የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) በቅንጅት የፈጠሩት ፓርቲ ነው። በነፃነት ፍቅሩ #EBC#Ethiopia#CEU