ለቱርክዬ ፕሬዝዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን በ2007 የተሰጠው ታሪካዊ ዕውቅና
********************
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለቱርክዬ ፕሬዝዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን የክብር ዶክትሬት መስጠቱ ይታወሳል
ምክንያት፦ ለአፍሪካ ሰላም፣ ለዲሞክራሲና ለኢኮኖሚ ዕድገት ላበረከቱት ጉልህ አስተዋጽኦ።
ዕውቅናው የተሰጠበት ቀን፦ ጥር 14 ቀን 2007 ዓ.ም
#EthiopianBroadcastingCorporation#Ebcdotstream#Ethiopia#Turkiye#Diplomacy
"ከአንካራ እስከ አዲስ አበባ፤ በሁለቱ ጥንታዊ ሀገራት መካከል ያለውን ትብብር ይበልጥ የሚያጠናክሩ እና ዘላቂ ትስስርን የሚያረጋግጡ ውጤታማ ውይይቶች እንዲኖሩን እመኛለሁ"
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
#EthiopianBroadcastingCorporation#Ebcdotstream#Ethiopia#PMAbiy#RecepTayyipErdoğan#Turkiye#Diplomacy
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለፕሬዝዳንት ረጅብ ጣይፕ ኤርዶዋን ደማቅ አቀባበል አደረጉ
*******************
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የቱርክዬ ሪፐብሊክ ፕሬዝዳንት ረጅብ ጣይፕ ኤርዶዋን በኢትዮጵያ ለሚያደርጉት ይፋዊ ጉብኝት ዛሬ በአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተገኝተው ተቀብለዋቸዋል።
ይህ ጉብኝት በቱርክዬ እና በኢትዮጵያ መካከል ያለውን እያደገ የመጣ ስትራቴጂካዊ አጋርነት የሚያጎላ ሲሆን፤ የኢትዮጵያን የዲፕሎማሲ ማዕከልነት ሚናም የሚያረጋግጥ ነው።
#EthiopianBroadcastingCorporation#Ebcdotstream#Ethiopia#PMAbiy#RecepTayyipErdoğan#Turkiye#Diplomacy
እንኳን ደህና መጡ!
የቱርክዬ ፕሬዝዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን ለይፋዊ የስራ ጉብኝት ኢትዮጵያ፣ አዲስ አበባ ገብተዋል፡፡
#EthiopianBroadcastingCorporation#Ebcdotstream#Ethiopia#PMAbiy#RecepTayyipErdoğan#Turkiye#Diplomacy
የቱርክዬ ፕሬዝዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን አዲስ አበባ ገቡ
**************
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለቱርክዬ ሪፐብሊክ ፕሬዝዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን ወደ ምድረ ቀደምቷ ሀገር ኢትዮጵያ እንኳን በደህና መጡ በማለት ሞቅ ያለ አቀባበል ማድረጋቸውን ገልጸዋል።
ይህ ታሪካዊ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት ከዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ባለፈ፣ በሁለቱ ጥንታዊ ሀገራት መካከል ያለውን "ጥልቅ የአጋርነት ጥንካሬ" የሚያንጸባርቅ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ ዋና መልዕክት፦
"ይፋዊ የስራ የጉብኝት ልውውጣችን በቱርክዬ እና በኢትዮጵያ መካከል ያለውን ጥልቅ የአጋርነት ጥንካሬ የሚያንጸባርቅ ነው። በአንካራ እና በአዲስ አበባ መካከል ያለውን ትብብር ይበልጥ የሚያጠናክሩ እና ዘላቂ ትስስርን የሚያረጋግጡ ውጤታማ ውይይቶች እንዲኖሩን እመኛለሁ።"
ይህ ጉብኝት በምሥራቅ አፍሪካና በዩራሺያ መካከል ያለውን የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካና የስትራቴጂካዊ ትስስር ወደ አዲስ ከፍታ ያሸጋግራል ተብሎ ይጠበቃል።
#EthiopianBroadcastingCorporation#Ebcdotstream#Ethiopia#PMAbiy#RecepTayyipErdoğan#Turkiye#Diplomacy
“130 ሚሊዮን ሕዝብ ያላት ሀገር የባሕር በር አጥታ ተዘግቶባት መኖር እንደሌለባት ከቱርክዬ ፕሬዚዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን ጋር ተወያይተናል” - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
**************************
"130 ሚሊዮን ሕዝብ ያላት ሀገር የባሕር በር አጥታ ተዘግቶባት መኖር እንደሌለባት እና ሀገራችን የባህር በር በሰላማዊ መንገድ ማግኘት የምትችልበት ሁኔታ ላይ እንዲያግዙ ከቱርክዬ ፕሬዚዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን ጋር ተወያይተናል” ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ፕሬዚዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን በብሔራዊ ቤተመንግሥት የጋራ መግለጫ እየሰጡ ይገኛሉ።
#EBC#ebcdotstream#Ethiopia#PMAbiy#RecepTayyipErdoğan#Turkiye#Diplomacy
ኢትዮጵያ እና ቱርክዬ በጋራ ለመፈፀም የተግባቡባቸው የስምምነት አጀንዳዎች እና ነጥቦች
**************
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከፕሬዚዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን ጋር በብሔራዊ ቤተመንግሥት በሰጡት የጋራ መግለጫ ሁለቱ ሀገራት በጋራ ለመፈፀም የተግባቡባቸውን የስምምነት አጀንዳዎች እና ነጥቦች ዘርዝረዋል።
I. የንግድ እና ኢኮኖሚ ትብብር
✅ የንግድ ልውውጥ መጠን፦ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የንግድ ልውውጥ ቢያንስ ወደ አንድ ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ እና ከዚያም በላይ ለማሳደግ ታቅዷል።
✅ የዘርፍ ብዝሃነት (Diversification)፦ የንግድ ግንኙነቱ በተወሰኑ ምርቶች ላይ ብቻ ሳይወሰን የተለያዩ የቢዝነስ ዘርፎችን እንዲያካትት ስምምነት ላይ ተደርሷል።
✅ የቱርክዬ ኢንቨስትመንት፦ ታዋቂ የቱርክዬ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ ኢንቨስት በማድረግ ለሀገር ውስጥ እና ለጠቅላላው የአፍሪካ ገበያ የሚሆኑ ምርቶችን እንዲያመርቱ እና ኤክስፖርት እንዲያደርጉ ድጋፍ ለማድረግ ተስማምተዋል።
II. የባህር በር እና ዲፕሎማሲያዊ ድጋፍ
✅ ኢትዮጵያ ያቀደችውን የ10.2 በመቶ ዕቅድ ለማሳካት የባህር በር ወሳኝ መሆኑ ተገልጿል።
✅ ለኢትዮጵያ ዕድገት ማነቆ (bottleneck) የሆነውን የሎጂስቲክስ ችግር ለመፍታት የባህር በር ቁልፍ መሆኑ ታምኖበታል።
✅ ኢትዮጵያ በሰላማዊ መንገድ የባሕር በር እንድታገኝ ቱርክዬ በዲፕሎማሲው መስኩ የራሷን ጫና በመፍጠር የበኩሏን ሚና እንድትጫወት ከስምምነት ተደርሷል።
III. የፀረ-ሽብር ትግል እና አካባቢያዊ ጉዳዮች
✅ ኢትዮጵያ እና ቱርክዬ በፀረ-ሽብር ትግሉ ዙሪያ በጋራ ለመሥራት ተስማምተዋል።
✅ የአየር ንብረት ለውጥን በተመለከተ ቱርክዬ ዘንድሮ የምታዘጋጀውን የኮፕ (COP) ስብሰባ በሚቀጥለው ዓመት ለኢትዮጵያ የምታስረክብ በመሆኑ፣ በዝግጅት ሂደት ውስጥ የልምድ ልውውጥ እና መደጋገፍ ለማድረግ ተስማምተዋል።
IV. ሥልታዊ እና ቀጣናዊ ግንኙነት
✅ አፍሪካ በቀጣይ 20 እና 30 ዓመታት ውስጥ የሚኖራትን ከፍተኛ የኢኮኖሚ ሚና ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ ቱርክዬ በአፍሪካ ዕድገት ውስጥ ያላትን የጂኦግራፊያዊ እና ኢኮኖሚያዊ ሚና እንድትወጣ መግባባት ላይ ተደርሷል።
✅ በኢትዮጵያ እና በቱርክዬ መካከል ያለውን ጥንታዊ ግንኙነት በመከባበር እና በመደጋገፍ ላይ ተመሥርቶ ይበልጥ ለማጠናከር መሪዎቹ ቃል ገብተዋል።
#Ethiopia#Turkiye#Diplomacy#AbiyAhmedAli#RecepTayyipErdoğan#EthiopianBroadcastingCorporation#EBC#EBCdotstream
"ኢትዮጵያ ለቀጣናዊ ሰላም እና መረጋጋት ያላት አስፈላጊነት ይበልጥ እያደገ መጥቷል" - ፕሬዚዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን
*********
የቱርክዬ ፕሬዚዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ መስኮች ላስመዘገቡት ስኬት “እንኳን ደስ አለዎት” በማለት መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።
ፕሬዚዳንት ኤርዶዋን ይህን ያሉት ዛሬ በብሔራዊ ቤተመንግሥት ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ጋር በመሆን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ነው።
ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት አዲስ አበባ የሚገኙት ፕሬዚዳንቱ፥ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ጋር በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የትብብር ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር የሚያስችሉ በርካታ ስምምነቶችን ማድረጋቸውን ገልጸዋል።
ስምምነቶቹ ባቡርን ጨምሮ የትራንስፖርት መሠረተ ልማት ማስፋፋት፣ የፋብሪካዎች ግንባታ፣ የኃይል ማስተላለፊያ መስመሮች ዝርጋታ እና የቱሪዝም ልማትን እንደሚያካትቱ አብራርተዋል።
ፕሬዚዳንት ኤርዶዋን ረጅም የሀገረ መንግሥት ታሪክ እና የተረጋጋ አስተዳደር ያላት ኢትዮጵያ ለቀጣናዊ ሰላም እና መረጋጋት አስፈላጊነቷ ይበልጥ እያደገ መጥቷል ብለዋል።
ቱርክዬ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ምዕተ ዓመታትን ያስቆጠረ ግንኙነት ይበልጥ ለማሳደግ ከፍተኛ ትኩረት እንደምትሰጥም አክለዋል።
በላሉ ኢታላ
#Ethiopia#Turkiye#Diplomacy#AbiyAhmedAli#RecepTayyipErdoğan#EthiopianBroadcastingCorporation#EBC#EBCdotstream
የአታቱርክ ፈር ቀዳጅነት እና የፕሬዝዳንት ኤርዶዋን የኢትዮጵያ ጉብኝት፤ የሁለቱ ታላላቅ ሀገራት አዲስ ምዕራፍ
***********************
በታሪክ ማኅደር ውስጥ አንዳንድ መሪዎች ሀገርን ያስተዳድራሉ፤ ጥቂቶች ደግሞ ሀገርን ዳግም ይፈጥራሉ። ሙስጠፋ ከማል አታቱርክ በቱርካውያን ልብ ውስጥ የነገሠው ዝም ብሎ መሪ ስለነበረ አይደለም፤ ሊጠፋ የነበረን ማንነት ከሞት አፋፍ መልሶ በጠንካራ መሠረት ላይ የገነባ “የሀገር አዳኝ” ስለሆነ እንጂ።
ዛሬም ድረስ በቱርክዬ መኖሪያ ቤቶች፣ በመንግሥት መሥሪያ ቤቶችና በገንዘብ ኖቶች ላይ ገዝፎ የሚታየው የእርሱ ምስል የናፍቆት ብቻ ሳይሆን የሉዓላዊነት ምልክት ነው።
ለ600 ዓመታት ዓለምን ሲያናውጥ የነበረው የታላቁ ኦቶማን ኢምፓየር ግርማ ሞገስ በአንደኛው የዓለም ጦርነት ማብቂያ ላይ አከተመለት።
በአራት ማዕዘን የተከበበችው ቱርክዬ በወራሪዎች እጅ ልትቀራመት፣ ስሟም ከታሪክ ገጽ ሊፋቅ ጫፍ ደርሶ ነበር። የውስጥ መከፋፈልና የውጭ ወረራ ሀገሪቱን እንደ እሳት ሲለበልቧት፣ ቱርካዊ ነኝ ማለት ብርቅ ሊሆን ጥቂት ቀርቶት ነበር።
በዚህ በጨለማ የተዋጠ የታሪክ ምዕራፍ ውስጥ ነበር ሙስጠፋ ከማል እንደ ብርሃን ብቅ ያለው። ማንም ይሳካለታል ብሎ ባልገመተበት ወቅት፣ ተስፋ የቆረጠውን ሕዝብ አስተባብሮና የወታደራዊ መኮንንነት ጥበቡን ተጠቅሞ በጋሊፖሊ ጦርነት ወራሪዎችን ድል በማድረግ የትንሣኤውን መንገድ መረቀ።
አታቱርክ ንጉሣዊውን (የሱልጣኔት) ሥርዓት በማስወገድ በ1923 ዓ.ም የቱርክዬ ሪፐብሊክን ሲመሠርት፣ ዓላማው ሥልጣን መያዝ ብቻ አልነበረም፤ የዘመናት የኋላ ቀርነት ሰንሰለትን ሰብሮ ሀገሩን ወደ ሥልጣኔ ማማ ማውጣት እንጂ።
እርሱ የፈጠራት ቱርክ በሃይማኖትና በዘር የተከፋፈለች ሳትሆን፣ በብሔራዊ አንድነትና በዴሞክራሲያዊ እሴቶች ላይ የቆመች ጠንካራ ሀገር ናት።
ሃይማኖትን ከፖለቲካ በመለየት፣ ኢንዱስትሪን በማስፋፋትና የትምህርት ሥርዓቱን በማዘመን ቱርክን በዓለም አቀፍ መድረክ የምትከበር ሀገር አደረጋት። ዛሬ የምናያቸው ግዙፍ ግድቦች፣ ዓለም አቀፍ የአየር ማረፊያዎችና የሥልጣኔ ተቋማት ሁሉ የእርሱ ራዕይ ፍሬዎች ናቸው።
ሕዳር 1 ቀን 1938 ዓ.ም አታቱርክ ከዚህ ዓለም በሞት ቢለይም፣ ዐሻራው ግን ሕያው ነው። በየዓመቱ በዚህ ዕለት በመላው ቱርክ ሕይወት ለሁለት ደቂቃ የቆመች እስክትመስል መኪኖች ይቆማሉ፣ ፋብሪካዎች ይዘጋሉ፣ ዜጎችም በዝምታ የሕሊና ጸሎት ያደርጋሉ። ይህ ዝምታ ለታላቁ መሪ የሚሰጥ የክብር ምስክርነት ነው።
ቱርካውያን ዛሬም ችግር ሲገጥማቸው የሚሰባሰቡበት፣ ብሔራዊ ጥቅማቸውን የሚለኩበትና አንድነታቸውን የሚያጸኑበት መለኪያቸው አታቱርክ ነው።
እርሱ ከቁልቁለት የታደጋት ሀገር ዛሬ የሥልጣኔ ጎዳናዋን በልበ ሙሉነት እየተጓዘች ትገኛለች። ሙስጠፋ ከማል አታቱርክ ሀገር ከውድቀት ተነስቶ እንዴት እንደሚገነባ ለዓለም ያሳየ የታሪክ ድንቅ ሥራ ነው።
ከአንድ ምዕተ ዓመት በፊት በአታቱርክ ብርቱ እጆች የታነጸችው ዘመናዊቷ ቱርክ፣ ዛሬ በዓለም አቀፉ መድረክ ገዝፋ የምትታይ የኃያልነት ተምሳሌት ሆናለች።
ይህች ከውድቀት ተነሥታ የሥልጣኔ ማማ ላይ የወጣች ሀገር፣ በታሪክ አጋጣሚዎቿና በጠንካራ መሠረቷ ምክንያት በዓለም ፖለቲካና ኢኮኖሚ ውስጥ ያላት ስፍራ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየናኘ መጥቷል። የዛሬዋ ቱርክ ትላንት አታቱርክ በዘራው የጥንካሬ ዘር እና ዛሬ በዓለም መድረክ በምታሳየው ተሰሚነት የብዙዎችን ቀልብ መሳቧን ቀጥላለች።
ይህንን የታላቅነት ግርማ የተላበሰች ሀገር የሚመሩት የቱርኪዬ ፕሬዚደንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን፣ ዛሬ በታሪካዊቷ ኢትዮጵያ ጉብኝት ያደርጋሉ።
የሁለቱ ታላላቅ ሀገራት መሪዎች መገናኘትም በምሥራቅ አፍሪካና በመካከለኛው ምሥራቅ መካከል ያለውን ስትራቴጂካዊ ወዳጅነት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋግራል ተብሎ ይታመናል።
በዚህ ጉብኝት ወቅትም የሁለቱን ሀገራት ዲፕሎማሲያዊና ኢኮኖሚያዊ ትሥሥር ይበልጥ የሚያጠናክሩ፣ ለቀጣናው ዕድገት ፋይዳ ያላቸው የሁለትዮሽ ስምምነቶች እንደሚፈረሙ ይጠበቃል።
#EBC#ebcdotstream#Ethiopia#turkiye
ኢትዮጵያና ቱርክዬ፦ በታሪክና በእምነት የተገመደው ወዳጅነት!
*********************
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና በኢትዮጵያ በይፋዊ የሥራ ጉብኝት ላይ የሚገኙት የቱርክዬ ፕሬዚዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን ዛሬ በአዲስ አበባ የሁለትዮሽ ውይይት ካደረጉ በኋላ የጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
ፕሬዚዳንት ኤርዶዋን በመግለጫቸው፥ ኢትዮጵያ በአፍሪካ የመጀመሪያው የእስልምና መዳረሻ እና የፍትሐዊው ንጉሥ ነጃሺ መገኛ መሆኗ ለሁለቱ ሀገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መጠናከር ትልቅ መሠረት መሆኑን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በእስልምና ታሪክ ያላት የላቀ ሚና ለቱርክዬ ሁሌም ትልቅ ትርጉም እንዳለው ፕሬዚዳንቱ አንስተው፤ ይህ ጥንታዊ እና ታሪካዊ ወዳጅነት ዛሬም በልማት እና በዲፕሎማሲያዊ ትብብር ደምቆ መቀጠሉን አክለዋል።
የቱርክዬ የልማት ትብብር ኤጀንሲ (TIKA) ታሪካዊውን የንጉሥ ነጃሺ መስጂድ እና የንጉሡን መካነ መቃብር ዕድሳት ማጠናቀቁን ጠቅሰው፤ ይህም የሁለቱን ሀገራት እና ሕዝቦች ታሪካዊ ትስስር ይበልጥ እንደሚያጠናክረው ተናግረዋል።
የቱርክዬ ማሪፍ ፋውንዴሽንም በሀገራቸው እና በኢትዮጵያ መካከል የትምህርትና የባህል ድልድይ በመሆን የሁለቱን ሀገራት ህዝቦች ይበልጥ የማቀራረብ ሥራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ፕሬዚዳንት ኤርዶዋን በመግለጫቸው አረጋግጠዋል።
በላሉ ኢታላ
#Ethiopia#Turkiye#Diplomacy#History#KingNajashi#RecepTayyipErdoğan#EthiopianBroadcastingCorporation#EBC#EBCdotstream
የኮሪደር ልማት ስራዎች በርካታ ከተሞችን እየለወጡ ይገኛሉ - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)
******************
የኮሪደር ልማት ስራዎች የተሻለ ሀገርን ለትውልድ የመገንባት አካል ሆነው በርካታ ከተሞችን እየለወጡ ይገኛሉ ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለፁ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ የትስስር ገጻቸው ባጋሩት መልዕክት፤ በሐዋሳ ከተማ በሁለተኛው ምዕራፍ የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ስራዎችን በዛሬው ዕለት ተመልክተናል ብለዋል።
የኮሪደር ልማት ስራዎች የተሻለ ሀገርን ለትውልድ የመገንባት አካል ሆነው በርካታ ከተሞችን እየለወጡ ይገኛሉ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አጠቃላይ ስራዎቹ እያደገ ለመጣው ከተሜነት ሀገርን ያዘጋጁ መሆናቸውንም ገልፀዋል።
#EthiopianBroadcastingCorporation#Ebcdotstream#Ethiopia#PMAbiy
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከላይቤሪያ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ቦካይ ጋር መከሩ
*****************
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከላይቤሪያ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ቦካይ ጋር ውይይት አድርገዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው፤ ከላይቤሪያ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ቦካይ ጋር ተገናኝተን በቴክኖሎጂ፣ ሰው ሰራሽ አስተውሎት እና በተለይም ኢትዮጵያ ለመመስረት ባቀደችው የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዩኒቨርሲቲ በተመለከተ የሁለትዮሽ ውይይት አድርገናል ብለዋል።
#EthiopianBroadcastingCorporation#Ebcdotstream#Ethiopia#PMAbiy